AM/Prabhupada 0114 - ክርሽና ተብሎ የሚጠራው አዋቂ ሁሉንም ነገር ሲቆጣጠር ይገኛል፡፡



Lecture -- Laguna Beach, September 30, 1972

በብሀገቨድ ጊታ ውስጥ እንዲህ ተብሎ ተገልፆልናል፡፡ "ዴሂኖ ስሚን ያትሀ ዴሄ ኮማራም ዮቫናም ጃራ ታትሀ ዴሀንታራም ፕራፕቲር ድሂራስ ታትራ ና ሙህያቲ (ብጊ፡ 2 13) እናንተም ሆናችሁ እኔ ወይንም ሁላችንም በዚህ በቁሳዊ ገላችን ውስጥ ተጠምደን እንገኛለን፡፡ እኔ መንፈስ ወይም ነፍስ ነኝ፡፡ እናንተም እንደዚሁ ነፍስ ናችሁ፡፡ የቬዲክ እውቀት መመሪያም ይኅው ነው፡፡ "አሀም ብራህማስሚ" "እኔ ብራህማን ወይም ነፍስ ነኝ፡፡" ይህም ማለት ሁላችንም ነፍስ ነን ማለት ነው፡፡ ነገር ግን "ፓራ ብራህማን" ወይንም ታላቁ ነፍስ አይደለንም፡፡ እርሱ ዓብዩ ጌታ ወይንም አብ ብቻ ነው፡፡ እኛ "ብራህማን" ወይንም የዓብዩ ጌታ ቅንጣፊ ወገን የሆንን ነፍስ ነን፡፡ ነገር ግን የበላይ ወይንም ታላቁ ነፍስ አይደለንም፡፡ የዓብዩ ጌታ ነፍስ የተለየ ነው፡፡ ለምሳሌ እናንተ አሜሪካኖች ናችሁ፡፡ ታላቁ የአሜሪካ መሪ ግን ፕሬዚደንት ኒክሰን ነው፡፡ ገና ለገና እንደ ፕሬዝደንት ኒክሰን አሜሪካዊ ሆናችሁ እና ፕሬዚደንት ኒክሰን ናችሁ ለማለት አይቻልም፡፡ እንደዚሁም ሁሉ እያንዳንዳችን "ብራህማን" ወይንም ነፍስ ልንሆን እንችላለን፡፡ ቢሆንም ግን "ፓራ ብራህማን" ወይንም ታላቁ ነፍስ ልንሆን አንችልም፡፡ ፓራ ብራህማን ሽሪ ክርሽና ወይንም አብ ብቻ ነው፡፡ "ኢሽቫራ ፓራማ ክርሽና" ( ብሰ 5 1) "ኢሽቫራ ፓራማ" ማለት የበላይ ተቆጣጣሪ ማለት ነው፡፡ እያንዳንዳችንም በተወሰነ መንገድ የመቆጣጠር ሀይል አለን፡፡ አንድ ሰው ቤተሰቡን ሊቆጣጠር ይችላል ወይንም ቢሮውን፣ ንግዱን ወይንም ተማሪዎቹን ሊቆጣጠር ይችላል፡፡ የሚቆጣጠረው ቢጠፋ እንኳን ውሻውን ሊቆጣጠር ይችላል፡፡ ሊቆጣጠረው የሚችለው ነገር ከሌለ የሚቆጣጠረው ውሻ በቤቱ ያስቀምጣል፡፡ ወይም ደግሞ ሌላ እንስሳ እንደ ድመት ሊያስቀምጥ ይችላል፡፡ በዚህም መንገድ ሁሉም ሰው ተቆጣጣሪ ለመሆን ይፈልጋል፡፡ ይህም እውነታ ነው፡፡ ዞሮ ዞሮ ግን የበላይ ተቆጣጣሪው ሁልግዜ ዓብዩ ጌታ ብቻ ነው፡፡ በዚህ ዓለም ላይ የበላይ ተቆጣጣሪ ነኝ የሚል ሁሉ በሌሎች ስር ሲተዳደር እናየዋለን፡፡ እኔ ተማሪዎቼን እቆጣጠር ይሆኖል፡፡ ቢሆንም ግን እኔ ደግሞ በመንፈሳዊ አባቴ ቁጥጥር ስር እገኛለሁ፡፡ ስለዚህ በዚህ ምድር ላይ ማናችንም ብንሆን "ፍፁም የበላይ የሆንኩኝ ተቆጣጣሪ ነኝ" ለማለት አንችልም፡፡ ስለዚህ በዚህ ምድር ላይ የበላይ ተቆጣጣሪ ነኝ የሚል ሁሉ ምንም እንኳን የተወሰነ የመቆጣጠር ሀይል ቢኖረውም እርሱ ራሱ በሌሎች ቁጥጥር ስር ነው፡፡ ዞሮ ዞሮ ግን የበላይ ተቆጣጣሪ በመሆንም በማንም ቁጥጥር ስር ያልሆነ ባለ ስልጣን ስታገኙ የህም ዓብዩ ጌታ ወይም ሽሪ ክርሽና ይሆናል፡፡ ሽሪ ክርሽናን ለመረዳት በጣም አዳጋች አይደለም፡፡ በተወሰነ መንገድ እያንዳንዳችን የመቆጣጠር ሀይል እንዳለን መገንዘብ ይኖርብናል፡፡ ቢሆንም ግን ሁላችንንም የሚቆጣጠር ሌላ ሀይል እንዳለም መገንዘብ ይኖርብናል፡፡ ይህም የበላይ ተቆጣጣሪ ሽሪ ክርሽና ተብሎ ይታወቃል፡፡ እርሱም ሁሉን የሚቆጣጠር ነው፡፡ ሆኖም ደግሞ በማንም ቁጥጥር ስር አይደለም፡፡ ይህም ዓብዩ ጌታ ነው፡፡ "ኢሽቫራ ፓራማ ክርሽና ሳትቺት አናንዳ ቪግራሀ አናዲር አዲር ጎቪንዳ ሳርቫ ካራና ካራናም" (ብሰ 5 1) ስለዚህ ይህ የክርሽና ንቃተ ማህበር ሳይንቲፊክ ነው፡፡ ስልጣን ያለው ማህበር ሲሆን ትምህርቱም ለማንም አቅም አዳም ለደረሰ ሰው ሊገባ የሚችል ነው፡፡ በዚህም የክርሽና ንቃት እንቅስቃሴ የትምህርት ፍላጎት ያደረባችሁ ከሆነ ጥቅም ልታገኙ ትችላላችሁ፡፡ ሕይወታችሁም ስኬታማ ሊሆን ይችላል፡፡ የሕይወታችሁም ዓላማ ግብ ሊደርስ ይችላል፡፡ ይህም የተረጋገጠ ነው፡፡ ስለዚህ ያቀረብነውን መፃህፍቶች ለማንበብ ሞክሩ፡፡ በርካታ መፃህፍቶችን አትመናል፡፡ ወደ ድርጅታችንም በመምጣት ተማሪዎቻችን በክርሽና ንቃት ብልፅግና በምን ደረጃ ላይ እንደደረሱ ለመረዳት ትችላላችሁ፡፡ ከእነርሱም ጋር በመጎዳኘት ብዙ እውቀት ለመቅሰም ትችላላችሁ፡፡ ለምሳሌ አንድ ሰው የሜካኒክ ስራ ለመልመድ ከፈለገ ወደ ፋብሪካ ውስጥ ገብቶ በመቀጠር ብዙ ለመማር ይችላል ፡፡ ከሰራተኞቹ እና ከሜካኒኮቹ ጋር በመጎዳኘት ቀስ በቀስ እርሱ ራሱ ሜካኒክ ወይም የቴክኖሎጂ ሰው ሊሆን ይችላል፡፡ እንደዚሁም ሁሉ የክርሽና ንቃትን ለማስተማር ብዙ ድርጅቶችን ከፍተናል፡፡ እነዚህም ድርጅቶች ለሁሉም እድል የሚሰጡ ናቸው፡፡ ይህም እውቀት የሚያስተምረው እንዴት ነፍስ ወደመጣችበት የመንፈሳዊ ዓለም ቤቷ ለመሄድ እንደምትችል ነው፡፡ ሚስዮናችንም ይህ ነው፡፡ ይህም ሳይንሳዊ እና ስልጣን ያለው የቬዲክ ድርጅት ነው፡፡ ይህንንም የቬዲክ እውቀት ያገኘነው በቀጥታ ከሽሪ ክርሽና ነው፡፡ እርሱም ዓብዩ ጌታ ወይንም አብ ነው፡፡ ይህም እውቀት የብሀገቨድ ጊታ እውቀት ነው፡፡ የብሀገቨድ ጊታንም እውቀት ምንም ያልተዛባ ትርጉም ሳንሰጠው ልክ እንዳለ አቅርበነዋል፡፡ ሽሪ ክርሽና በብሀገቨድ ጊታ ውስጥ እርሱ ራሱ ዓብዩ ጌታ እንደሆነ ገልፆልናል፡፡ እኛም ይህንኑ መልእክት ሳናዛባ በቀጥታ ተርጉመን አቅርበነዋል፡፡ ይህም ዓብዩ ጌታ ሽሪ ክርሽና መሆኑን በመግለፅ ነው፡፡ የቀየርነውም ነገር የለም፡፡ በብሀገቨድ ጊታ ውስጥ ሽሪ ክርሽና "የኔ አገልጋይ ሁኑ" ብሎ ገልፆልናል፡፡ "ሁልግዜ እኔን አስታውሱ፡፡ ስግደትም አድርጉ፡፡ እጅ ንሱ" ስለዚህ እኛም የሰው ልጆችን የምናስተምረው ይህንኑ መልእክት ነው፡፡ "ሽሪ ክርሽናን ሁል ግዜ አስታውሱ" ይህም ቅዱስ ስምን በመዘመር ነው፡፡ "ሀሬ ክርሽና ሀሬ ክርሽና ክርሽና ክርሽና ሀሬ ሀሬ ሀሬ ራማ ሀሬ ራማ ራማ ራማ ሀሬ ሀሬ" ይህንንም ቅዱስ ስም ዘወትር በመዘመር ሽሪ ክርሽናን በቀላሉ ለማስታወስ ትችላላችሁ፡፡